እግዚአብሔርን ማወቅ

በኢየሱስ ማመን ታላቅ እምነት ነው?

 

እግዚአብሔርን ማወቅ የሚቻልበት መንገድ

በኢየሱስ ማመን ኢ ምክኒያታዊ ነውን?

ስለ ኢየሱስ ማንነት ከሚነሱ አመለካከቶች ጋር ስንገጣጠም ብዙዎቻችን የምናስበው እነዚህ ሃሳቦች የተለጠጡና በምክኒያት ላይ ያልተመሰረተ የእምነት እርምጃ የሚጠይቁ እንደሆኑ ነው፡፡ 

ነገር ግን በኢየሱስ ላይ ያለ እምነት እና ትንሳኤው ( ከሞት መነሳቱ) ተዓማኒ ብቻ ሳይሆን እጅግ ምክንያታዊ ነው ብላችሁስ? "ይህ ክርስቲያናዊ ድረ ገጽ ስለሆነ እንዲህ ማለትህ አያስገርምም" ትሉኝ ይሆናል። 

እንደዛ ማለታችሁ ትክክል ነው።

ያ ግን እኔ ትክክል አይደለሁም ማለት ነው? 

ኢየሱስ ማን ነበር?

ኢየሱስ ያስተምር የነበረው ትምህርት አንኳር ነጥብ በማንነቱ ላይ ያተኮረ ነበር።

እስቲ ኢየሱስን በህይወቱ ላይ ያነጣጠረው ክስ በቀረበበት ወቅት እንመልከተው።

"እርሱ ግን ዝም አለ አንዳችም አልመለሰም። ደግሞ ሊቀ ካህናቱ ጠየቀውና። የቡሩክ ልጅ ክርስቶስ አንተ ነህን? አለው። ኢየሱስም፦ እኔ ነኝ፤ የሰው ልጅም በኃይል ቀኝ ሲቀመጥ በሰማይም ደመና ሲመጣ ታያላችሁ አለ። ሊቀ ካህናቱም ልብሱን ቀደደና። ከእንግዲህ ወዲህ ምስክሮችን ምን ያስፈልገናል? ስድቡን ሰማችሁ፤ ምን ይመስላችኋል? አለ። እነርሱም ሁሉ፡- ሞት ይገባዋል ብለው ፈረዱበት።" 

(ማርቆስ ወንጌል 14:61 - 64)

ይህ የጥንት ጊዜ ንግግር በግልፅ እንደሚያሳየው ኢየሱስ ራሱን አምላክ ነኝ በማለቱ በሞት እንዲቀጣ ፈልገው ነበር። ኢየሱስ ስለራሱ የተናገራቸውና ለሞቱ ምክኒያት የሆኑ ወጣ ያሉ ንግግሮቹ እንደሚከተለው ቀርበዋል፡-

  • ኢየሱስን ማወቅ እግዚአብሔርን ማወቅ ነው። ( ዮሐንስ ወንጌል 8፡19 ፣ 14፡7 )

  • ኢየሱስን ማየት እግዚአብሔርን ማየት ነው። ( ዮሐንስ ወንጌል 12፡ 45 ፣ 14፡9) 

  • ኢየሱስን ማመን እግዚአብሔርን ማመን ነው፡፡ ( ዮሐንስ ወንጌል 12:44 ፣ 14፡1 ) 

  • ኢየሱስን መቀበል እግዚአብሔርን መቀበል ነው፡፡ ( ማርቆስ ወንጌል 9:37)

  • ኢየሱስን መጥላት እግዚአብሔርን መጥላት ነው፡፡ ( ዮሐንስ ወንጌል 15:23)

  • ኢየሱስን ማክበር እግዚአብሔርን ማክበር ነው። ( ዮሐንስ ወንጌል 5:23)

አታላይ፣ እብድ፣ አፈ ታሪክ ወይም ጌታ

እነዚህን የኢየሱስ የማንነት ይገባኛል ባይነት ስንመለከት የምናገኘው አራት አማራጮችን ብቻ ነው። ኢየሱስ ወይ ውሸታም፣ ወይ እብድ ፣ ወይ አፈታሪክ ፣ ወይም ደግሞ በርግጥ ነኝ እንደሚለው ጌታ ነው።

አታላይ፡ ኢየሱስ ራሱን ከእግዚአብሔር ጋር ሲያስተካክል እየዋሸ ሊሆን ይችላል። ውሸታም ከሆነ ግን ኢየሱስ ታላቅ የግብረገብ መምህር ሊሆን አይችልም። 

እብድ፡ ኢየሱስ ራሱን የሚያታልል እብድ ሊሆን ይችላል። ነገር ግን ህይወቱ ምንም ዓይነት የአዕምሮ መዛባት እንደነበረበት አያመለክትም፡፡

አፈ ታሪክ፡ ምናልባትም የኢየሱስ ተከታዮች እርሱ ራሱ አምላክ ነኝ ብሏል የሚለውን ሃሳብ አቀናብረውት ሊሆን ይችላል። ይህ በአሁኑ ጊዜ በብዛት የምንሰማው አመለካከት ነው። 

ኢየሱስ አምላክ ነው የሚለውን ሃሳብ የፈጠሩት ምናልባትም የኢየሱስ ተከታዮች ሊሆኑ ይችላሉ፡፡

ነገር ግን በአርኬዎሎጂ ጥናት የተመዝገቡ ግኝቶች መሰረት ተመራማሪዎች ወንጌላት በሙሉ የተፃፉበት ጊዜ ከመጀመሪያው ክፍለ ዘመን መባቻ እጅግ ቀድመው እንደሆነ እንዲገነዘቡ አድርጓቸዋል፡፡ 

ታዲያ የዚህ ትርጉም ምንድነው? ወንጌላት በተጻፉበት ወቅት ኢየሱስን ያዩና ትምህርቶቹን የሰሙ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በህይወት ነበሩ። 

ተራ አፈ ታሪክ ቢሆን ኖሮ እነዚህ የዓይን እማኞች በቀላሉ ሊቃወሙትና ሊሸሩት ይችሉ ነበር። 

ለምሳሌ ጆን ኤፍ. ኬኔዲ አምላክ ነው የሚል መፅሐፍ አሁን ባለንበት ዘመን ተፃፈ እንበል። ይህንን ማንም ሊቀበል አይችልም፤ እንዲያውም ዛሬ ድረስ በህይወት ያሉ በዚያ ጊዜ የነበሩ ሰዎች "ጆን ኤፍ. ኬኔዲን አውቀው ነበር፤ አምላክ ነኝ ብሎ ተናግሮ አያውቅም፡፡" ብለው ይናገሩ ነበር።

ነገር ግን ተመራማሪዎች በወንጌላት ላይ የተጠቀሱትን ታሪኮች ትክክለኛነት የሚቃወም አንድም የዓይን እማኝ መረጃ ሊያገኙ አልቻሉም።

ጌታ፡ ከላይ የተጠቀሱት አማራጮች ትክክል ካልሆኑ የሚቀረው ብቸኛ አማራጭ ኢየሱስ አምላክ ነኝ ማለቱ እውነት ነው የሚለው ነው። 

ታዲያ ኢየሱስ አምላክ ነኝ ስላለ ምን ይደረግ?

ሐዋርያው ጳውሎስ ኢየሱስ ከሙታን ካልተነሳ እምነታችን ከንቱ ነው ብሎ ተናግሮ ነበር (1ኛ ቆሮንቶስ 15፡14)፡፡

የኢየሱስ ከሞት መነሳት የአምላክነቱ ማረጋገጫ ነው ብለው በማመናቸው ሁሉም ሐዋርያት (በግዞት ከነበረው ከአንዱ በቀር) ለሞት ተዳርገዋል፡፡

በሞት እንዳይቀጣ የትኛውም ሐዋርያ ይህንን ሊክድ ይችል ነበር፤ ነገር ግን አንድም የካደ አልነበረም። 

ኢየሱስ ሞቶ ሳይሆን ራሱን ስቶ ቢሆንስ?

ኢየሱስ የሞተው በህዝብ ፊት በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ነበር። 

በዚያ ጊዜ የነበረው አገዛዝ የኢየሱስ ሞት ምክኒያት እግዚአብሔርን መሳደቡ ነው ብሎ ነበር። 

ኢየሱስ ግን የሞተው ለሃጢአታችን እንደሆነ ተናግሯል። 

የሞተው በብዙ ስቃይ ውስጥ ሆኖ እጅና እግሮቹ በተሰቀሉበት መስቀል ላይ በሚስማር ተቸንክረው ቀስ በቀስ ትንፋሽ በማጣት ነበር፡፡ 

መሞቱንም ለማረጋገጥ ጎኑን በጦር ወግተውት ነበር፡፡

በድኑም በግምት 46 ኪ.ግ. በሚመዝን ሽቱ በተነከረ የተልባ እግር ጨርቅ ተጠቅልሎ ከዓለት በተዋቀረ መቃብር ውስጥ ተቀመጠ። የመቃብሩን መግቢያ ደህንነት ለመጠበቅ ከ 1.5 - 2 ቶን ክብደት ባለው ድንጋይ ተዘግቶ ነበር። ኢየሱስ በህይወት እያለ በሦስት ቀናት ውስጥ ከሙታን እንደሚነሳ በግልፅ በመናገሩ መቃብሩን እንዲጠብቁ የሰለጠኑ የሮም ወታደሮች ዘብ እንዲቆሙ ተደርጎ ነበር። መቃብሩም የመንግስት ንብረት እንደሆነ የሚያመለክት የሮም መንግስታዊ ማህተም በመግቢያው በር ላይ ተደርጎ ነበር።

ነገር ግን ከሦስት ቀናት በኋላ የኢየሱስ በድን ጠፋ። በመቃብሩ የነበረው ከፈኑ ብቻ ነበር። መግቢያ በሩን ዘግቶ የነበረው ትልቅ ድንጋይ ከበሩ በርቀት ላይ ተንከባሎ ነበር። 

ራሱን ስቶ ነበር እንጂ እየሱስ ከሙታን አልተነሳም የሚለው ቲዎሪ በኢየሱስ ትንሳኤ ላይ በተቃውሞ ከተነሱት ቲዎሪዎች የቅርብ ጊዜው ነው። 

እስኪ ይህንን ሃሳብ አንድ ጊዜ እንመልከተው፡፡ ኢየሱስ ራሱን ስቶ በህይወት እያለ ተቀበረ እንበል። ከዚያም ራሱን ከሳተበት ይነቃል። በነቃ ጊዜ ሊያደርግ የሚችላቸው ነገሮች፡-

  1. በእርጥበት በተሞላው መቃብር ውስጥ ያለምግብና ያለ ውሃ ሦስት ቀናት መቆየት ይኖርበታል። እስኪ ከተገረፍክ ፣ ከተሰቀልክና ከተወጋህ በኋላ ይህንን ስታደርግ አስበው።

  2. ከተከፈነበት ጨርቅ ራሱን ማላቀቅና እጅግ ትልቅ የሆነውን ድንጋይ ከመቃብሩ አፍ ላይ መግፋት ይኖርበታል፡፡

  3. በጥበቃ ላይ የነበሩትን የሮማውያን ወታደሮች ማሸነፍ አለበት።

  4. በሚስማር ተቸንክረው በነበሩት ባዶ እግሮቹ ለብዙ ኪሎ ሜትሮች መጓዝ አለበት።

በክርስቶስ ትንሳኤ የማያምነው ጀርመናዊው ተቺ ዴቪድ ስትራውስ እንኳን ኢየሱስ ራሱን ስቶ ነበር የሚለውን ቲዎሪ እንዲህ ሲል ያጣጥለዋል፡-

"ደካማና ታማሚ ሆኖ ፣ የህክምና እርዳታ ፣ የቁስል ማሰሪያ ፋሻ፣ ጥንካሬና ርህራሄ መቀበል የሚሻውና በስቃይ የተሸነፈው ሰው ከመቃብር በከፊል እንደሞተ ሰው ሆኖ ወደ ደቀ መዛሙርቱ መጥቶ ሞትንና መቃብርን ድል የነሳ የህይወት ልዑል እንደሆነ እንዲያስቡ ሊያደርግ ፈፅሞ አይቻለውም፡፡"

ነገር ግን እስኪ ኢየሱስ በርግጥ ይህንን አድርጓል ብለን እናስብ። 

አንድ ትልቅ ስራ ግን ይጠብቀዋል። ተከታዮቹ ይህንን ውሸት እንዲቀበሉና በዚህም ለሞት ራሳቸውን አሳልፈው እስከሚሰጡ ድረስ ይህንን ውሸት እንዲያሰራጩ በስፋት ማሳመን ይኖርበታል፡፡

ነገር ግን ኢየሱስ ይህንን አድርጓል ብሎ የተናገረ ከተከታዮቹ መሐል አንድም ሰው የለም። 

ታዲያ እኔም የዚህ ሁሉ መረጃ አሳማኝነት ነው በኢየሱስ ከማመን ይልቅ አለማመን ኢ ምክኒያታዊ ነው ብዬ እንዳስብ ያደረገኝ። 

ታዲያ ምን ታስባላችሁ?

ኢየሱስን በተመለከተ የሚነሱ ተደጋጋሚ ጥያቄዎችን ለመመልከት እዚህ ይጫኑ።

 

 

©ግሬት ኮሚሽን ሚኒስትሪ ኢትዮጵያ። መብቱ በህግ የተጠበቀ ነው።